Pages

Tuesday, May 22, 2018

የእስራኤልና ኢራን ፍጥጫ





እስራኤል የኢራን በሶሪያ መመሸግ ደስታን አይሰጣትም።ኢራን በሶሪያ ምድር የጦር ቀጣናዋን ማደራጀቷም «ሳይታሰብ ጥቃት እንድትፈፅም»ምቾት ይሰጣታል በሚል ከአካባቢው መራቋን አጥብቃ ትሻለች። የኑውክሌር መርሀ ግብሯንም ቢሆን ከበጎው ይልቅ ለክፉ አላማ የሚቀመር መሆኑን ስታምን ፕሬዚዳንት ሀሳን ሮሀኒ በአንፃሩ ይህ ፈፅሞ ከእውነት የራቀ ስለመሆኑ ይሟገታሉ።
በእርግጥም ከሁለት ዓመታት በፊት በነበረው ስምምነት መሰረት ኢራን የዩራንየም ክምችቷን መቀነስን ጨምሮ የኑውክሌር ፕሮግራሟን ለማቆም ከበለፀጉት አገራት ጋር ስምምነት ፈፅማለች።ይህ ግን ኢራን ቃሏን ስለመጠበቋ አንዳች ማረጋገጫ የለንም ለሚሉት እስራኤላውያን ፈፅሞ አይዋጥም።
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ቢሆን ስምምነቱንም ሆነ ኢራንን የሚመለከቱት በእስራኤል መነፅር ነው።በተለይ በኒውክሌር መርሃ ግብር እንደ ቤኒያሚን ኔታኒያሁ እርሳቸውም ቢሆን አያምኗትም። እናም በምርጫ ቅስቀሳቸው ቃል በገቡት መሰረት አገራቸው ከኢራን ጋር የፈረመችውን ስምምነት ለመቅደድ ብዙ ጊዜ አልጠበቁም። ከሰሞኑ ኢራን የተወሰነውን የስምምነቱን አካል እንዳላከበረች በመግለፅ ፊርማቸውን በይፋ አንስተዋል።

ወትሮም ቢሆን በኢራን ላይ በምታንፀባርቀው አቋም ደጋፊ ስትናፍቅ የቆየችው እስራኤል ታዲያ የልዕል ሃያሏ አገርን ከስምምነቱ መውጣት በፍፁም ፈገግታ ነበር የተቀበለችው።
ከቀናት በፊት ደግሞ«በጎላን ኮረብታዎች በሚገኙ ይዞታዎቼ ላይ ከኢራን በኩል የሮኬት ጥቃት ተፈፅሞብኛል»በሚል ከባድ የአፀፋ ምላሽ ሰጥታለች።ከ10 ዓመት በኋላ እጅጉን ከባዱ ድብደባ ነው በተባለለት በዚህ ጥቃትም ሶሪያ ውስጥ የሚገኘው የኢራን ወታደራዊ ሰፈሮችና የጦር መሳሪያዎች ማከማቻዎችን አውድማለች። ጥቃቱም «በሕልውናዬ ላይ ለሚመጣ ሁሉ ቅንጣት ትዕግስት እንደሌለኝና፤ቀይ መስመሩን የሚያልፍ ሁሉ እንደሚቀጣ የሚያሳይ ነው» ስትል ተደምጣለች።
አሜሪካ ራሷን ከኢራን የኒውክሌር ስምምነት ባወጣች ማግስት የተወሰደው ይህን እርምጃ ተከትሎም ከሁሉ በላይ በሁለቱ አገራት መካከል ከባድ የተባለ ጦርነት እንደሚኖር አረንጓዴ መብራት ያሳየ መሆኑን ብዙዎች መናገር ጀምረዋል።የሁለቱ አገራት ቀውስም ወደ ጎረቤት አገራት በተለይም ወደ ሶሪያና ሊባኖስ እንዳይዛመት፤ ብሎም በአገራቱ ጎን በሚሰለፉ ኃይሎች እንዳይባባስና ዓለም አቀፍ ቀውስን እንዳያስከትል ተሰግቷል።
በተለይ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ስምምነት አገራቸውን ማስወጣታቸው የሁለቱን አገራት ጦርነት አይቀሬ አድርጎታል መባል ጀምሯል። የዋሽንግተን ፖስት ዘጋቢዋ አማንዳ ኤሪክሰን ትንታኔም ይህን አመላክቷል። እርግጥም ፕሬዚዳንቱ ከስምምነቱ አገራቸውን ካስወጡ በኋላ በእስራኤልና በኢራን መካከል ፍጥጫው ጦፏል። በተለይም እስራኤል ወታደሮቿን በተጠንቀቅ ሰድራለች።በሁለቱ አገራት መካከል መሰል ፍጥጫ ሲካሄድ የመጀመሪያው ባይሆንም የአሁኑ ግን እጅጉን የጦዘ ነው። እናም በቅርብ ጊዜያት ውስጥ በሁለቱ አገራት መካከል የጡንቻ ፍተሻ መኖሩ ሳይታለም የተፈታ ነው ትላለች።
የኤሪክሰን ሃሳብ የሚደግፉት በስኮትላንዱ አንድሪውስ ዩኒቨርሲቲ የመካከለኛው ምስራቅ አበይት ክንውን ተመራማሪው ፕሮፌሰር አሊ አንሳሪም፤የትራምፕ ውሳኔ ሁሉም የሰላም ሂደቱን ጥላሸት መቀባቱን በመጠቆም፤ ለኢራንና እስራኤል የሰላም ተቃራኒን ይዞ እንደሚመጣ አስምረውበታ ል።
በተለይም የትራምፕ አስተዳደር ከኢራን ተቃዋሚ ሆኖ መሰለፍ ከዚህ ቀደም የነበሩ የሰላም ሂደቶችን በማቆርፈድ አገሪቱ ሌሎች አማራጮችን እንድትከተልና ይበልጥ ቁጡ እንድትሆን ያደርጋታል የሚሉም በርካቶች ሆነዋል። ከእነዚህም አንዱ ቀደም ሲል የገባቸውን ቃል በመሰረዝ የኑውክሌር ፕሮግራሟን ዳግም መጀመር መሆኑ ተመላክቷል።
የሲቢሲ ተንታኟ ማርጋሬት በርናርም፣ የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሞሃመድ ጃቫድ ዛሪፍ አሜሪካ በኢራን ላይ ከባድ ማዕቀብ ለመጣል የሚዳዳት ከሆነ አገሪቱ አፃፋውን ለመስጠት የሚያስችላት በርካታ አማራጮች እንዳላት መናገራቸውን አስታውሳለች።የኢራን ቀጣይ የመጫወቻ ካርድም የኒውክሌር ጉዳይ መሆኑን አመላክታለች።
ይህ ከሆነ ታዲያ በሲንጋፖር የራርትማን የትምህርት ተቋም የመካከለኛው ምስራቅ ጉዳዮች ተመራማሪ የሆነው ጄምስ ዶርሲ እንደገለፀው፤ በመካከለኛው ምስራቅ የኒውክሌር ፉክክር በይፋ ይጀመራል።ውጤቱም ከእስራኤል ኢራን ጦርነት ባሻገር ቀጣናዊ ጦርነት ለማስነሳት ዋነኛ ምክንያት ይሆናል።
በኢራን የቀድሞው የእንግሊዝ አምባሳደር ሰር ሪጃርድ ዳልታን በአንፃሩ፤ «የኒውክሌር ስምምነቱን በሚመለከት ሌሎች ባለድርሻዎች በቀጣይ የሚያሳዩት አቋም የጦርነቱን እጣ ፈንታ ይውስነዋል ነው» ያሉት። የአሶሽየትድ ፕሬስ ሳራ ኤልዴፕ እንዳተተችውም፤ ምንም እንኳን አሜሪካ ከስምምነቱ ሯሷን ብታገልም አሁንም ቢሆን ስምምነቱ እንደፀና ነው። ሆኖም ኢራን ለስምምነቱ ቀጣይነት ቃሏን መጠበቋ ብቻውን ዋስትና አይሰጣትም። በተለይ የአሜሪካ በኢራን ላይ ከባድ ማዕቀብ ካወጀች የቴሄራን መንግስት እጀጉን ይንገዳገዳል።እስራኤል በአንፃሩ ይበልጥ ትፈረጥማለች። «እናም የኒውክሌር ስምምነቱ ህልውና በሁለቱ አገራት ቀጣይ እርምጃና በዓለም የነገ እጣ ፈንታ ላይ የመወሰን እድሉ እጅጉን ግዙፍ ነው»ብላለች።
አሁን ላይ የሚሰሙ ጭምጭምታዎችም አሜሪካ በኢራን ላይ ከባድ ማዕቀብ ለመጣል እየተሰናዳች መሆኑን ነው። እስራኤልም ቢሆን ከኢራን በተመለከተ በማንም አይነት መልኩ በኒውክሌር ጉዳይ መደራደር እንደማትፈልግ አስታውቃለች። ይህ ታዲያ ውጥረቱን በሰላማዊ መንገድ በድርድር ለመፍታት ሃሳብ ላላቸው ተስፋ አስቆራጭና መጪውን በስጋት እንዲመለከቱት ምክንያት ሆኗል።
የሮይተርሱ ኦማር ሳንድኪ፤የሁለቱ አገራት ጦርነት ወደ ሌሎች አገራት የመዛመት እድል እንዳለው አትቷል።በተለይ ከአስራ ሁለት ዓመት በፊት የእስራኤልና የኢራን አጋር እንደሆነ በሚገለፀው ሄዝቦላ መካከል ለተካሄደው ፍልሚያ የጦር ሜዳ ሆና ያገለገለችው ሊባኖስ በቀላሉ እንደሚደርስ አስፍሯል።
በእርግጥም ሁለቱ አገራት ጦር ከመዘዙ አሜሪካ ኢራን በየመን የሚገኙ አማፂያንን ትደግፋለች ስትል የምትከሰውን ሳውዲ አረቢያን ጨምሮ አሜሪካና ሩሲያን ከጀርባው ያስከተለ እጅግ አስከፊ የተባለ ጦርነት መከሰቱ ጥርጥር አይኖረውም።
በተለይ በእስራኤልና በኢራን ፍጥጫ ለሁለቱም ወዳጅ የሆነችው ሩሲያ ከሁሉም በላይ ወሳኝ አገር ትሆናለች።ይህ ከሆነ ታዲያ ሩሲያ ለማናቸው ታደላለች የሚሉ ጥያቄዎች መነሳታቸው እርግጥ ነው። በዚህ ረገድ እንደ ዘጋርዲያኑ ፒተር ባውሞንት እንዳሰፈረው ትንታኔም፤በእርግጥ ሩሲያ በሁለቱ አገራት ጦርነት እጅግ ወሳኝ አገር ናት።እስራኤል ኢራን ላይ ድብደባ እንዳትፈፅም ለማድረግ ከሩሲያው ፕሬዚዳንት የሚጠበቀው አንድ የስልክ ትዕዛዝ ብቻ ነው።ይሁንና የአሜሪካና እስራኤል ጥምር ጦር ኢራን ላይ ለአንድ ዓላማ በጋራ እንዲቆም ፍላጎት የላትም።«አሜሪካ እስከሌለችበትም የእስራኤልና የኢራን ፍጥጫ ለሞስኮው መንግስት ብዙም አይረብሸውም ነው»ያለው።
በእርግጥ በኢራንና እስራኤል ፍጥጫ አሜሪካ ጣልቃ እንደማትገባ ማንም ማስተማመኛ የለውም። አሁን ባለው ሁኔታ ግን አሜሪካና እስራኤል የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው የተባባሉ መስለዋል።ለኢራንም ቢሆን በፍልስጤም ወገን ሃማስ፤ በሊባኖስ ሄዝቦላ በኢራቅ በኩል ደግሞ የሺያት ወታደሮች ከጎኗ ናቸው።ይህን የጦርነት አሰላለፍ በትኩረት የቃኙ በርካቶች ግን ጦርነቱ ከሚሆን ባይሆን ይሻላል እያሉ ናቸው።
ታምራት ተስፋዬ

No comments:

Post a Comment