Pages

Tuesday, May 22, 2018

አዲስ ተስፋ የፈነጠቀው የሁለቱ ኮሪያዎች መሪዎች ግንኙነት

አዲስ ተስፋ የፈነጠቀው የሁለቱ ኮሪያዎች መሪዎች ግንኙነት
የሰሜን ኮሪያ ፕሬዚዳንት ኪም ጆንግ ኡንና የደቡብ ኮሪያ አቻቸው ሙን ጃኤ-ኢን በፓንሙንጆም ድንበር የሰላም፣ የብልፅግናና የውህደት ስምምነትን ከተፈራረሙ በኋላ ተቃቅፈው ይታያሉ

 

ዓለማችን ዓርብ ሚያዚያ 19 ቀን 2010 ዓ.ም. የሰሜንና የደቡብ ኮሪያ መሪዎች የሁለቱን አገሮች ጦርነት በይፋ ለማቆም ያደረጉትን ዓይነት ስምምነት ያየችው ሁለት ጊዜ ብቻ ነው፡፡ እ.ኤ.አ. በ1938 የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ኔቪል ቻምበርሌይንና የጀርመን ቻንስለር አዶልፍ ሒትለር ሲጨባበጡ፣ እ.ኤ.አ. በ1985 የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬገንና የሶቪየት ኅብረት የመጨረሻው መሪ የነበሩት ሚካኤል ጎርባቾቭ በእሳት ዙሪያ ተቀምጠው ሲነጋገሩ የታዩ ጊዜ ነበር ዓለም ተመሳሳይ ስምምነትና የሰላም ጅማሮን ያየችው፡፡
ዓለም በሶሪያና በየመን ጦርነት እየታመሰች ባለችበት በዚህ ወቅት፣ ከወደ ፓንሙንጂየም የተሰማው የሰሜን ኮሪያ መሪ ኪም ጆንግ ኡንና የደቡብ ኮሪያው መሪ ሙን ጃኤ-ኢን መገናኘት ዜና ለብዙዎች ተስፋ ሰጪ የሆነ ክስተት ነበር፡፡

ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ማብቂያ በኋላ ከአንድ አገርነት ወደ ሁለት አገርነት የተቀየሩት ሰሜንና ደቡብ ኮሪያ የመከፋፈል ምክንያታቸው በዋናነት የርዕዮተ ዓለም ጉዳይ ነበር፡፡ ከጃፓን የ35 ዓመታት አገዛዝ በኋላ ተከፋፍለው በመሯቸው አሜሪካና ሶቪየት ኅብረት የተቃኙ የርዕዮተ ዓለም አስተሳሰቦችን ይከተላሉ፡፡ ሰሜን ኮሪያ በሶቪየት ኅብረት ጎራ የነበረችው የሶሻሊስት አስተሳሰብን ስትከተል፣ በአሜሪካ ወገን ያለችው ደቡብ ኮሪያ ደግሞ ካፒታሊዝምን የሙጥኝ ብላ እስካሁን አለች፡፡
አዲስ ተስፋ የፈነጠቀው የሁለቱ ኮሪያዎች መሪዎች ግንኙነት
የደቡብና የሰሜን ኮሪያ ልዑካን ፓንሙንጆም በተባለችው ወታደራዊ ነፃ ድንበር ተገናኝተው እጅ ለእጅ ሲጨባበጡ



ይኼን ተከትሎ ሁለቱ ኮሪያዎች በይፋዊ እ.ኤ.አ. በ1950 ጦርነት ከመጀመራቸው አስቀድሞ በነበሩት ሁለት ተከታታይ ዓመታት በተደጋጋሚ ግጭቶች ውስጥ ይገቡ ነበር፡፡ እ.ኤ.አ. በ1950 ግን የሰሜን ኮሪያ ወታደሮች የደቡብ ኮሪያን ድንበር ጥሰው ወረራ በመፈጸማቸው የኮሪያ ጦርነት በይፋ ተጀመረ፡፡
ከሦስት ዓመታት የኮሪያ ጦርነት በኋላ አራት ኪሎ ሜትሮች ያህል ክፍት የወታደራዊ ነፃ ቀጣና በመተው፣ የተኩስ አቁም ስምምነት በማድረግ ጦርነቱ ተገታ፡፡ ይሁን እንጂ የሁለቱ አገሮች ወታደሮች መሣሪያዎቻቸውን ደግነው በተጠንቀቅ ቆመው ይታያሉ፡፡ የኮሪያ ጦርነት በተኩስ አቁም ስምምነት ብቻ ይፋ የሆነ የጦርነት ማብቂያ ሳይደረግበት ለ65 ዓመታት ቆይቷል፡፡
እ.ኤ.አ. ኤፕሪል 27 ቀን 2018 የሁለቱ አገሮች መሪዎች በወታደራዊ ነፃ ቀጣና ተገናኝተው ጦርነቱን በይፋ ለማብቃት ስምምነት ለማድረግ መቃረባቸውን አስታወቁ፡፡ ይኼንንም ክስተት ለሁለት አሠርት ዓመታት በከፍተኛ ጉጉት ሲጠባበቁና የማይመስል ይባል የነበረውን ውይይት ለማምጣት ሲጥሩ የነበሩት የደቡብ ኮሪያው የደኅንነት ኃላፊ ሱህ ሁን፣ ሁለቱ መሪዎች ሲገናኙ እምባቸውን በመሃረባቸው ሲያደርቁ ታይተዋል፡፡
መሪዎቹ በሞቀ ፈገግታ ሲጨባበጡ፣ ከጉልበት ትንሽ ዝቅ የሚለውን የድንበር አካፋይ ግድግዳ እየተሸጋገሩ በሰሜንና በደቡብ ኮሪያ መሬቶች ላይ ሲረማመዱ ያዩ ብዙዎቹ እውነትም በኮሪያ ልሳነ ምድር ሰላም ሊመጣ ነው የሚል ተስፋ እንዲሰንቁ አድርጓቸዋል፡፡
ከዚህ አለፍ ብሎም የሰሜን ኮሪያው መሪ ኪም ጆንግ ኡን በግንቦት ወር የኑክሌር ጣቢያቸውን እንደሚዘጉ ቃል መግባታቸውና የኑክሌር ሚሳይሎች ሙከራ ላለማድረግ መወሰናቸው ትልቅ ዕርምጃ እንደሆነና ይህ ክስተት ከሁለቱ መንትያ አገሮችና ከአካባቢያቸው ደኅንነት ባለፈ ሁለቱ አገሮች ሊዋሀዱ የሚችሉበት አጋጣሚ ሊፈጠር ይችላል የሚሉ ግምቶች እንዲሰሙ አድርገዋል፡፡
አዲስ ተስፋ የፈነጠቀው የሁለቱ ኮሪያዎች መሪዎች ግንኙነት
ሁለቱ መሪዎች ሁለቱን አገሮች በለያየው ወታደራዊ መለያ መስመር ላይ ሲጨባበጡ



ሆኖም በሶሻሊስትና በካፒታሊስት ኢኮኖሚ ውስጥ ሲተዳደሩ ለቆዩትና የምጣኔ ሀብታቸው ደረጃ የሰማይና የምድር ያህል የተራራቁት የሁለቱ ኮሪያዎች ውህደት ዕውን መሆን አጠራጣሪ ነው፡፡ በሰሜን ኮሪያ በድህነት ተቆራምደው የሚኖሩ ዜጎች የደቡብ ኮሪያ በሮች ቢከፈቱላቸው፣ ሙሉ በሙሉ ፈልሰው ወደ ይገባሉ የሚል መላምት የውህደት ዕቅዱ ላይ እንከን ሊሆን ይችላል የሚሉ አሉ፡፡
በሌላ በኩል የሰሜን ኮሪያው አምባገነናዊ አስተዳደር ወደ ዴሞክራሲያዊ አስተዳደር ለመምጣት ያለው ቁርጠኝነት አጠራጣሪ መሆኑ፣ ብሎም በሁለት ርዕዮተ ዓለም ውስጥ የኖሩ ሕዝቦች መካከል የሀብትም ሆነ የአስተሳሰብ አንድነትን ለማምጣት ከባድ መሆኑ ውህደቱን ከተግባራዊነት ይልቅ ህልም እንዲመስል አድርገውታል፡፡
ይሁን እንጂ የሁለቱ ኮሪያዎች መሪዎች በ65 ዓመታት ውስጥ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ለመጀመርያ ጊዜ ተገናኝተው ላደረጉት ስምምነት፣ ምሥጋና ለመውሰድ የአሜሪካውን ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕን የቀደማቸው የለም፡፡
የሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ስምምነቱን ሲያደንቁ፣ ፕሬዚዳንት ትራምፕ ደግሞ የኋይት ሀውስ ዘጋቢዎች ራት ግብዣ ላይ ከመገኘት ይልቅ ለደጋፊዎቻቸው ንግግር ማድረግን በመምረጥ፣ በኮሪያ ልሳነ ምድር የተፈጠረውን ሰላም ሲያደንቁና ጥረታቸው እንደሆነ ሲያወሱ ተደምጠዋል፡፡ ደጋፊዎቻቸውም ‹ኖቤል፣ ኖቤል› በማለት ፕሬዚዳንቱ ለኖቤል ሽልማት ብቁ ናቸው በማለት እያሞካሹ ሲጮሁላቸው ተስተውሏል፡፡
አዲስ ተስፋ የፈነጠቀው የሁለቱ ኮሪያዎች መሪዎች ግንኙነት
 ሰሜንና ደቡብ ኮሪያውያን ቤተሰቦች ሲገናኙ እንዲህ ዓይነት ስሜት ይፈጠራል

በግንቦት ወር መጨረሻ እንደሚገናኙ የሚጠበቁት ኪም ጆንግ ኡንና የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የት እንደሚገናኙ ግልጽ የሆነ መረጃ ባይኖርም፣ በሁለቱ ኮሪያዎች የታየው የሰላም ስምምነት፣ ብሎም የሰሜን ኮሪያው መሪ የኑክሌር ጦር መሥሪያ ሙከራ ለማቆምና የኑክሌር ጣቢያቸውን ለመዝጋት መወሰናቸውን ማሳወቃቸው ለዚያ ስብሰባ ቅድመ ሁኔታዎችን ማመቻቸታቸው ሊሆን እንደሚችል የሚጠቁሙ ተመልካቾች አሉ፡፡
ሰሜን ኮሪያን፣ ደቡብ ኮሪያን፣ ቻይናንና አሜሪካን ያካተተ የአራትዮሽ ጉባዔ እንዲዘጋጅ ከኮሪያዎቹ ፍላጎት እንዳለም እየተነገረ ነው፡፡ ይሁንና የሰሜን ኮሪያ የኑክሌር ጦር መሣሪያዎች ያስገኛል ስትል የቆየችው ጃፓን ከዚህ ውይይት የመገለል ሥጋት እያደረባት መጥቷል፡፡ የጃፓን ፕሬዚዳንት ሺንዞ አቤ ከሳምንት በፊት በአሜሪካ ያደረጉት ጉብኝት ከዶናልድ ትራምፕ ጋር በዚሁ ጉዳይ ዙርያ ለመነጋገር እንደሆነም የሚጠቁሙ አሉ፡፡ 
አዲስ ተስፋ የፈነጠቀው የሁለቱ ኮሪያዎች መሪዎች ግንኙነት
ደቡብ ኮሪያውያን የሰሜን ኮሪያ ፕሬዚዳንት ወደ ድንበር ከተማዋ ፓንሙንጆም ሲደርሱ በቴሌቪዥን የቀጥታ ሥርጭት ሲከታተሉ

No comments:

Post a Comment