Pages

Friday, June 1, 2018

የመጠጥ ውሃ እጥረት የኢትዮጵያ ስጋ


ኢትዮጵያ ከሰሐራ በታች ካሉ ዝቅተኛ የመጠጥ ውሃ ካላቸው አገራት አንዷ ስትሆን ለመጠጥ ውሃ ከምታመርተው ውስጥ 39 ከመቶው አገልግሎት ሳይሰጥ ይባክናል፡፡ በቀጣይም የመጠጥ ውሃ እጥረት ያጋጥማታል፡፡
ዶክተር ኢንጅነር አብዱላ ከማል በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የውሃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሳይንቲፊክ ዳይሬክተር ሲያብራሩ፤ በኢትዮጵያ ራሱን በዓመቱ የሚተካው የገፀ ምድር ውሃ 122 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ ነው፡፡ ተከታታይ ጥናት ባይደረግም የከርሰ ምድር ውሃው 36 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ እንደሆነ ይገመታል፡፡ ታዲያ በዓለም አቀፍ ስሌት አንድ ሰው በዓመት የሚያገኘው የውሃ መጠን ከ1ሺ700 እስከ 1000 ሜትር ኪዩብ ከሆነ ወደፊት የውሃ እጥረት ይኖራል ፡፡

በአመት ከ500 ሜትር ኪዩብ በታች መጠቀም የእጥረቱ ማሳያ ነው፡፡ ከበቂ በላይ ውሃ አለ ለማለት ደግሞ አንድ ሰው በዓመት 1ሺ700 ሜትር ኪዩብ በላይ ውሃ ሊደርሰው ይገባል፡፡ በዚህ ቀመርም አንድ ኢትዮጵያዊ በዓመት 1ሺ220 ሜትር ኪዩብ ውሃ ያገኛል፡፡ በመሆኑም የኢትዮጵያ የውሃ ሀብቷ የበዛም ያነሰም አይደለም፡፡ ነገር ግን በውሃ ሀብቷ የምትታማ ባትሆንም ከውሃ እጥረት እንዳላመለጠች ግን ዶክተር ኢንጅነር አብዱላ ይናገራሉ፡፡
ዶክተር ኢንጅነር አብዱላ በአሁኑ ወቅት የአየር ንብረት ለውጥና ሙቀት መጨመር አሳሳቢ መሆኑን በመጠቆም ሙቀት ሲጨምር ትነት ስለሚኖር በአፍሪካ በተለይም ደግሞ ኢትዮጵያ የምትገኝበት ከሰሐራ በታች ያሉ አገራት በዚህ ችግር ክፉኛ ይጎዳሉ፡፡ አንዳንድ አካባቢዎችን ምድረበዳ የማድረግ አጋጣሚም ይፈጠራል፡፡ ይህ ደግሞ ዝናብ እንኳ ቢኖር መትነን እንጂ ወቅቱን ጠብቆ ወደ ከርሰ ምድር የመግባት ዕድል የለውም፡፡
ተመራማሪው እንደሚሉት፤ በአገሪቱ በርካታ መስኖ ግድቦችም ሲገነቡ በኮንክሪት የተሞሉ ባለመሆናቸው ስርገትን መከላከል አለመቻሉ፣ የከርሰ ምድር ውሃን ከመጠን በላይ መሳብና መጠቀም፣ የህዝብ ቁጥር መጨመር በህገ ወጥ መንገድ ፋብሪካዎችና ኢንዱስትሪዎች የውሃ ሀብትን መበከላቸው፤ በቂና ወጥነት ያለው ጥናትና መፍትሄ አለመኖር፤ የሰለጠነ የሰው ኃይል እጥረት ለችግሩ መባባስ አስተዋፅኦ አድርገዋል፡፡
ወጥ ያልሆነ የውሃ ሀብት ስርጭት በቦታና በጊዜ ተመጣጣኝ አለመሆኑ ሌላኛው ችግር ነው፡፡ ለአብነት ከቦታ አኳያ ሲታይ በአገሪቱ ካሉት 12 ተፋሰሶች 122 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ ውሃ ይመረታል፡፡ ይሁንና 80 ከመቶ ውሃ የሚመነጨው ከአባይ፣ ባሮ አኮቦ፣ ተከዜ እና ኦሞ ጊቤ ተፋሰሶች ነው፡፡ በዚህ አካባቢ የሚኖረው የአገሪቱ ህዝብ ደግሞ ከ40 እስከ 45 ከመቶ የሚሆኑት ብቻ ናቸው፡፡ ከ50 እስከ 55 የሚሆነው ህዝብ የሚኖረው ደግሞ ውሃው ከሚመነጭበት አካባቢ ነው፡፡ ይህ የውሃ ስርጭት፣ የህዝቡ አሰፋፈርና አኗኗር ተመጣጣኝ አለመሆኑ ኢትዮጵያን በእጅጉ ይፈትናታል፡፡ ከጊዜ አኳያ ሲመዘንም የአገሪቱ ወንዞች በክረምት ወቅት በርካታ በበጋው ደግሞ ትንሽ ውሃ ያመነጫሉ፡፡ 
የሥነ-ምድር ተመራማሪና በባህርዳር ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት ዶክተር ሰይፉ አድማሱ በበኩላቸው፤ በአሁኑ ወቅት አገሪቱ ጥቅም ላይ እያዋለች ያለው የውሃ ሀብት ሙሉ ለሙሉ በቴክኖሎጂ የተደገፈ አይደለም፡፡ የአየር ፀባይና በዓመቱ ያለው የውሃ የፍሰት መጠን ተቀያያሪ በመሆኑ ከ40 እስከ 50 ከመቶ የሚሆነው ውሃ ወደ ከርሰ ምድር እንዳይገባ ያደርገዋል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በርካታ የአገሪቱ ወንዞች ድንበር አቋርጠው የሚፈሱ በመሆናቸው ከፍተኛ የውሃ ፍሰት በሚኖርበት የክረምት ወቅት ውሃውን በአገር ውስጥ አምቆ ለመጠቀም የሚያስችል ስልት አልተነደፈም፡፡
የህዝብ ቁጥር በየጊዜው እየጨመረ በመሄዱም ከፍተኛ የምግብ ፍጆታን ለማምረት የገፀ ምድር ውሃ በብዛት ጥቅም ላይ ስለሚውልና ወደ ከርሰ ምድር መግባት ያለበት ውሃ ባለመግባቱ እጥረት ይከሰታል፡፡
በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የምርምር፤ ማህበረሰብ አገልግሎትና የቴክኖሎጂ ሽግግር ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ምህረት ዳናንቶ ኢትዮጵያ በቀጣይ የውሃ እጥረት ያጋጥማታል የሚለው ጉዳይ ብቻ ሳይሆን በአሁኑ ወቅትም የውሃ ሀብቱ እያላት ችግር ውስጥ መሆኗን ይናገራሉ፡፡
እንደ ተመራማሪው ማብራሪያ፤ በዓለም አቀፍ ስሌት መሰረት አንድ ሰው በቀን ከ120 እስከ 250 ሊትር ውሃ መጠቀም አለበት፡፡ ይሁንና በኢትዮጵያ አንድ ሰው በቀን የሚጠቀመው አማካይ ውሃ ከ30 እስከ 60 ሊትር ነው፡፡ ከአገሪቱ ህዝብ ውስጥም ከ40 እስከ 60 ከመቶ የሚሆነው ውሃ በበቂ ሁኔታ አያገኝም፡፡ ንጹህ የመጠጥ ውሃ የሚያገኙትም 56 ከመቶ ብቻ ናቸው፡፡
ስምጥ ሸለቆን የመሳሰሉት ተፋሰሶች በውስጣቸው አይረንና ፍሎራይድ የበዛባቸው በመሆናቸው ጥቅም ላይ እየዋለ ያለው አነስተኛ መሆኑ፣ የግብርና ሥራው ኋላቀርነትና የእንስሳት ቁጥር ከፍተኛ ቁጥር ላይ መድረሱ፣ የህዝብ ቁጥር መጨመርና በከተሞች አካባቢ ያሉ የውሃማ አካላት ለብክለት መዳረጋቸው ችግሩን እያባባሱ ያሉ ክስተቶች መሆናቸውን ዶክተር ምህረት ያብራራሉ፡፡
በውሃ፤ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስቴር የኢትዮጵያ የከተሞች የመጠጥ ውሃና ፍሳሽ አገልግሎቶች ፌዴሬሽን ዋና ዳይሬክተር አቶ ሙክታር አህመድ፤በርካታ አካባቢዎች የሚኖሩ ሰዎች ከዋና ከተማ ረጅም ርቀት በመጓዝ የመጠጥ ውሃ ለመፈለግ ይገደዳሉ፡፡ ለአብነት በጎንደር ከተማ የመጠጥ ውሃ የክምችት ሥፍራ ለማግኘት እስከ 40 ኪሎ ሜትር ድረስ ፍለጋ ይጓዛሉ፡፡ ይህም የውሃ ጉዳይ በቀጣይ አሳሳቢ ስለመሆኑ መልዕክት እየሰጠ ነው ይላሉ፡፡
ከውሃ፤ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ የ2008 ዓ.ም የአገሪቱ መጠጥ ውሃ አቅርቦት የሚያገኘው 62 ከመቶ የሚሆነው ህዝብ ብቻ ነው፡፡ በ2009 ዓ.ም ደግሞ 65ነጥብ7 ከመቶ የሚሆኑት ብቻ ናቸው ንጹህ ውሃ የሚያገኙት፡፡
ከዓለማችን 75 ከመቶ በውሃ የተሸፈነ ሲሆን ለሰዎች ጥቅም የሚሰጠው ሦስት ከመቶ ብቻ ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ ሁለት ሦስተኛው ውሃ ያለው በዓለማችን ደቡብ እና ሰሜን ንፍቀ ክበብ በግግር በረዶ መልክ ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ የሰው ልጅ የሚጠቀመው ሦስት ከመቶ ውሃ ውስጥ አንድ ሶስተኛውን ብቻ ነው፡፡ በዚህ ስሌት መሠረት ውሃ እጅግ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ ስለመጠየቁ ማሳያ ነው፡፡
ዶክተር ኢንጅነር አብዱላ እንደሚሉት፤ አገሪቱ አሁን ያለውን የውሃ አጠቃቀም ካላዘመነች፣80 ከመቶ የሚሆነው ውሃ ከሚመረትባቸው አራቱ ተፋሰሶች ውሃን ወደሌላ አካባቢ ካላሰራጨች፣ ንፁህ ውሃን በሚፈለገው መጠን ብቻ መጠቀም ካልቻለች፣ ውሃን ደጋግሞ በማጣራት በመልሶ መጠቀም ስልት ካልተገለገለች፣ የተቀናጀ የውሃ አስተዳደር መከተልና ትልልቅ ውሃ በሚጠቀሙ ኢንዱስትሪዎች ላይ ህጋዊ አሰራሮች ተግባራዊ ካላደረገች በቅርብ ዓመታት ውስጥ ለከፋ የውሃ ችግር ትጋለጣለች፡፡
ዶክተር ሰይፉ አድማሱ በበኩላቸው፤ የህዝብን ቁጥር መመጠንና የአጠቃቀም ፖሊሲ ካልተዘጋጀ፣ የህዝቡ የአኗኗር ዘይቤ ካልተሻሻለ፣ ወንዞች ከዓመት ዓመት መደበኛ ፍሰት እንዲኖራቸው ተፈጥሮን መንከባከብ ካልተቻለ፣ በትንሽ ቦታ ላይ ብዙ ምርት የሚመረትበት የግብርና ቴክኖሎጂ ተግባራዊ ካልተደረገ፣ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ በሳይንሳዊ ዘዴ ካልተደገፈ የውሃ እጥረት ችግሩ የከፋ ይሆናል፡፡
በርግጥም በክረምት ወቅት የሚመጣውን የውሃ መጠን በትልልቅ ግድቦች በማከማቸት መጠቀም ካለተቻለ፣ በግብርናው መስክ ጠብታ መስኖ የመሳሰሉትን በማላመድ ተግባር ላይ ካልዋለ፣ ያለውን የውሃ ሀብት በጥናት ላይ በመመስረት ካልለማ፣ የከርሰ ምድር ውሃ እንዲያገግም ካልተደረገ፣ ደመናን ወደ ውሃ በመቀየርና ሌሎች አማራጭ የውሃ ምንጮችን የመጠቀም ባህል ካልዳበረ ኢትዮጵያን የውሃ እጥረት ይፈትናታል፡፡
ዜና ትንታኔ
ክፍለዮሐንስ አንበርብር

No comments:

Post a Comment